በጋምቤላ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂዎች ድንበር አቋርጠው በመግባት ጥቃት አደረሱ::

በጋምቤላ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂዎች ድንበር አቋርጠው በመግባት ጥቃት አደረሱ
በጋምቤላ ከደቡብ ሱዳን የሚነሱ የሙርሌ ጎሳ ታጣቂዎች ድንበር አቋርጠው በመግባት ጥቃት ማድረሳቸውን የጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሰላምና ፀጥታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ኡቶዉ ኡኮት ገለፁ።
ኃላፊው አክለውም ለኢፌድሪ መከላከያም ድንበር አቋርጦ የገባ የታጠቀ ኃይል እንዳለ በማሳወቅ ድጋፍ እንዲያደርጉላቸው መጠየቃቸውን ይናገራሉ።
አቶ ኡቶዉ እንደሚሉት በጋምቤላ በዚህ ሰዓት በጋ ስለሆነ እና ክልሉን ከደቡብ ሱዳን ጋር የሚያጋራው ድንበር ሰፊና ክፍት ስለሆነ የታጣቂዎች የመግባትና የመውጣት አዝማሚያ አለ። የሙርሌ ታጣቂዎች ባለፈው ወር ድንበር አቋርጠው በመግባት ከኑዌር ዞን ጂካ ወረዳ አንድ ሕፃን መውሰዳቸውን ያስታውሳሉ። እንዲሁም ከዚሁ ወረዳ 150 ከብት እና 234 ፍየሎችንም ዘርፈዋል ያሉት ኃላፊው ከሳምንት በፊት ጆር በሚባል አካባቢ ከአካባቢው ሚሊሻ ጋር የተኩስ ልውውጥ አድርገው ከእነርሱ ወገን ሰው መጎዳቱን ይናገራሉ።
አቶ ኡቶዉ ክልሉ በአሁኑ ሰዓት ልዩ ኃይሉንና ሚሊሻ በመጠቀም ሰላምና ፀጥታ የማስከበር ስራውን እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በቅርብ የሙርሊ ጎሳ ታጣቂዎች ጥቃት ባደረሱባቸው አካባቢዎች መሄዳቸውን የሚናገሩት ኃላፊው የአካባቢው ነዋሪ ስጋት እንዳለበት መታዘባቸውን ገልፀዋል። ክልሉ የነዋሪውን ስጋት ለማስወገድ እና ቀዬውን ለቅቆ እንዳይሄድ የተለያዩ የማረጋጋት ስራዎችን መስራታቸውንም ተናግረዋል።
የሙርሌ ጎሳ ታጣቂዎች ከሁለት ዓመት በፊት፤ በኑዌር ዞን እና አኙዋ ዞኖች ገብተው 234 ሕፃናት አፍነው ሲወስዱ፣ ከአንድ መቶ ሰባ በላይ ሰዎች ደግሞ ሕይወታቸውን ማጣታቸው ይታወሳል። በወቅቱ ከ2ሺህ በላይ ከብቶች መውሰዳቸውንም ኃላፊው ጨምረው ያስታውሳሉ።
በወቅቱ የኢፌድሪ መከላከያ ኃይል ወደ ደቡብ ሱዳን በመግባትና ታጣቂዎቹ የሚኖሩበት አካባቢ ላይ ጥቃት በመፈፀም ታፍነው ከተወሰዱት ሕፃናት መካከል ከ100 ሕፃናት በላይ ወደ ቤተሰቦቻቸው መልሷል። ቀሪዎቹ ግን የደረሱበት አልታወቀም።(ቢቢሲ)

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *