አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር በመሆን ተሾሙ::

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 10፣ 2011 (ኤፍ.ቢ.ሲ) አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር በመሆን ተሾሙ።

ጨፌ ኦሮሚያ በዛሬው እለት ባካሄደው አራተኛ አስቸኳይ ስብሰባው ነው አቶ ሽመልስ አብዲሳን የክልሉ ምክትል ርእሰ መስተዳድር አድርጎ የሾመው።

በምክትል ርእሰ መስተዳድርነት የተሾሙት አቶ ሽመልስ የርእሰ መስተዳድርነት ስራውን የሚሰሩ መሆኑም ታውቋል።

የኦሮሚያ ክልል ርእሰ መስተዳድር የሆኑት አቶ ለማ መገርሳ በዛሬው እለት የኢፌዴሪ የሀገር መከላከያ ሚኒስትር በመሆን መሾማቸውን ተከትሎ ነው ጨፌው አቶ ሽመልስን በምክትል ርእሰ መስተዳድርነት የሾመው።

አቶ ሽመልስ ዛሬ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር ሆነው እስከሚሾሙ ድረስ የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ሀላፊ በመሆን ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

የቀድሞ የኦሮሚያ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ ለማ መገርሳ በጉባዔው ላይ ባስተላለፉት መልእክት፥ “የህዝባችን ትግል እውን እስኪሆንና ፍላጎታቸው ከግቡ እስኪደርስ ድረስ ህዝቡ የወከለኝ በመሆኑ በህብረት እና በአንድነት የተጣለብንን የታሪክ አደራ እንወጣለን” ብለዋል።

‘እኔም የሚጠበቅብኝን ጠንክሬ እሰራለሁ’ ሲሉም አቶ ለማ በጉባዔው ላይ ተናግረዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *